ለሠላት ሊሟሉ የሚገቡ መስፈርቶች ምንድን ናቸው?

  1. ከሐደስና ከነጃሳ መጥራት፡፡ ዝርዝር ገለፃውን አሳልፈናል (ገጽ፣ 91 ተመልከት)
  2. ሀፍረተ ገላን መሸፈን

ሀፍረተ ገላን በአጭርነትና ወይም በስስነት የሰውነት ክፍሎችን የማያጋልጥና የማያሳይ በሆነ ልብስ መሸፈን የግድ ነው፡፡

ሀፍረተ ገላ ሦስት ዓይነት ነው፡፡

ለሴት፡ ሰላት ለመስገድ የደረሰች ሴት ሀፍረተ ገላ ከፊቷና ከመዳፎቿ በስተቀር ሰውነቷ በሙሉ ነው፡፡

ለሕፃን፡ ትንሽ ሕፃን ልጅ ሀፍረተ ገላው ሁለቱ ብልቶቹ ብቻ ናቸው፡፡

ወንድ፡ የደረሰ ወንድ ሀፍረተ ገላ ከእምብርቱ እስከ ጉልበቱ ድረስ ነው፡፡

አላህ (ሱ.ወ)፡- «የአደም ልጆች ሆይ (ሀፍረተ ገላችሁን የሚሸፍኑትን) ጌጦቻችሁን በመስገጃው ሁሉ ዘንድ ያዙ፡፡» ይላል፡፡ (አል

አዕራፍ 31) ሀፍረተ ገላን መሸፈን ከመጌጥ ትንሹ ደረጃ ነው፡፡ ‹‹በመስገጃው ሁሉ›› ማለት በየሠላቱ ማለት ነው፡፡

 ሙስሊም ሴት፣ በሠላት ውስጥ ከፊቷና ከመዳፎቿ በስተቀር ሌላውን ሰውነቷን በሙሉ መሸፈን አለባት፡፡ .

  1. ወደ ቂብላ መቅጣጨት ወይም መዞር :

አላህ (ሱ.ወ)፡- «ከየትም (ለጉዞ) ከወጣህበት ስፍራ ፊትህን ወደ ተከበረው መስጊድ አቅጣጫ አዙር፡፡» ብሏል፡፡ (አል በቀራ 149)

 አላህ (ሱ.ወ)፡- «ሶላት በምእመናን ላይ በጊዜያት የተወሰነች ግዴታ ናትና፡፡» ይላል፡፡ (አል ኒሳእ 103)

  • የሙስሊሞች የስግደት አቅጣጫ የተከበረው ካዕባ ነው፡፡ እሷን የገነባት የነብያት አባት የሆነው ኢብራሂም(ዐ.ሰ) ነው ፡፡ ነብያት ወደርሷ የአምልኮ ጉዞ (ሐጅ) አድርገዋል፡፡ እርሷ የማትጠቅም የማትጎዳም ድንጋይ እንደሆነች እናውቃለን፡፡ ግን አላህ (ሱ.ወ) ሙስሊሞች በሙሉ ወደ አንድ አቅጣጫ በመዞር አንድ እንዲሆኑ፣ ስንሰግድ ወደርሷ እንድንዞር ወይም እንድንቅጣጭ አዞናል፡፡ ስለሆነም፣ ወደ ካዕባ በመዞራችን የአላህ ባርነታችንን እንገልጻለን፡፡
  • አንድ ሙስሊም ሲሰግድ ካዕባን ፊት ለፊት የሚመለከታት ከሆነ ወደርሷ ፊቱን ማዞር ግድ ነው፡፡ ከርሷ በርቀት የሚገኝ ሰው ደግሞ ወደ መካ አቅጣጫ መዞሩ በቂ ነው፡፡ በሚቅጣጭ ጊዜ ከካዕባ አቅጣጫ ትንሽ ማዘንበሉ ወይም መዞሩ ችግር የለውም፡፡ ነብዩ (ሰ.ዐ.ወ)፡- «በምስራቅና በምዕራብ መሐከል ያለ በሙሉ የሠላት አቅጣጫ (ቂብላ) ነው፡፡›› ብለዋል፡፡ (አል ቲርሚዚ 342)
  • ልክ የተቀሩት ግዴታዎች በመቸገር ምክንያት ግዴታነታቸው እንደሚነሳ ሁሉ፣ በበሽታ ወይም በሌላ ምክንያት ወደ ካዕባ መዞር ላልቻለም ግዴታነቱ ይነሳለታል፡፡ አላህ (ሱ.ወ)፡- «አላህንም የቻላችሁትን ያክል ፍሩት፡፡» ይላል፡፡ (አል ተጋቡን 16)
  1. የሠላት ወቅት መግባት

ይህ ለሠላት ትክክለኛነት መስፈርት ነው፡፡ ወቅቷ ከመግባቱ በፊት የተሰገደች ሠላት ትክክለኛ አትሆንም፡፡ ከወቅቷ ማዘግየትም የተከለከለ ነው፡፡ አላህ (ሱ.ወ)፡- «ሶላት በምእመናን ላይ በጊዜያት የተወሰነች ግዴታ ናትና፡፡» ይላል፡፡ (አል ኒሳእ 103)

ወቅት በመግባት ዙሪያ በተወሰኑ ነገሮች ላይ እርግጠኛ መሆን ያስፈልጋል፡፡

  • ሠላትን በመጀመሪያው ወቅት ላይ መስገዱ በላጭ ነው፡፡
  • ሠላትን በወቅቷ መስገድ ግዴታ ነው፡፡ በማንኛውም ምክንያት ቢሆንም ሠላትን ማዘግየት ክልክል ነው፡፡
  • በእንቅልፍ ወይም በመርሳት ምክንያት ሠላት ያለፈው ሰው ባስታወሰ ጊዜ ፈጥኖ መስገድ አለበት፡፡

 አምስቱ የግዴታ ሠላቶችና ወቅቶቻቸው

አላህ (ሱ.ወ) በሙስሊሞች ላይ በቀንና በሌሊት ውስጥ አምስት ሠላቶችን ግዴታ አደርጓል፡፡ እነኚህ ሠላቶች የሃይማኖት ምሶሶዎች ናቸው፡፡ ግዴታነታቸውም እጅግ አጽንዖት የተሰጠው ጉዳይ ነው፡፡ ለነርሱም የሚከተሉትን ወቅቶች አድርጎላቸዋል፡፡

የፈጅር ሠላት፡ ሁለት ረካዓ ነው፡፡ ወቅቱ የሚጀምረው ጎሕ ከሚወጣበት ጊዜ ሲሆን፣ በአድማስ ላይ ብርሃን ሲፈነጥቅ ወይም ጨለማ መገፈፍ ሲጀምር ይከሰታል፡፡ የሚያበቃው ደግሞ ፀሐይ ስትወጣ ነው፡፡

የዙህር ሰላት፡ አራት ረከዓ ነው፡፡ ወቅቱ የሚጀምረው ፀሐይ ከመሐል አናት በምታዘነብልበት ጊዜ ሲሆን የሚያበቃው ደግሞ የእያንዳንዱ ነገር ጥላ ከራሱ ቁመት ጋር ሲስተካከል ነው፡፡

የዐሥር ሠላት፡ አራት ረከዓ ነው፡፡ ወቅቱ የሚጀምረው የዙህር ወቅት ካበቃበት ጊዜ ጀምሮ ሲሆን ይኸውም የእያንዳንዱ ነገር ጥላ ከራሱ ቁመት ጋር ሲስተካከል ነው፡፡ የሚያበቃው ደግሞ ፀሐይ ስትጠልቅ ነው፡፡ አንድ ሙሰሊም ይህችን ሠላት፣ የፀሐይ ብርሃን ጮራ መድከምና መገርጣት ሳይጀምር ፈጠን ብሎ ሊሰግድ ይገባዋል፡፡

የመግሪብ ሠላት፡ ሦስት ረከዓ ነው፡፡ ወቅቱ የሚጀምረው ፀሐይ ከጠለቀችበትና ፍንጣቂዋ ከአድማስ ላይ ሲወገድ ወይም ሲደበቅ ነው፡፡ የሚያበቃው ደግሞ ከፀሐይ መጥለቅ በኋላ የሚታየው ቀዩ ወጋገን ሲጠፋ ነው፡፡

የዒሻእ ሠላት፡ አራት ረከዓ ነው፡፡ ወቅቱ የሚጀምረው ቀዩ ብርሃን ከጠፋበት ቅጽበት ነው፡፡ የሚያበቃው እኩለ ሌሊት ላይ ነው፡፡ አስቸጋሪ ሁኔታ በሚገጥምበት ጊዜ ጎህ እስኪ ቀድ ባሉት ሰዓቶችም ውስጥ ሊሰገድ ይችላል፡፡

አንድ ሙስሊም የሰላትን ወቅቶች በተመለከተ በወቅቶች ሰሌዳ መጠቀም ይችላል ነገር ግን ወደ ሰላት ለመግባት እሱን የመመልከት ግዴታ የለበትም