በመላእክት የማመን ትርጓሜ

.

ይህ የመላእክትን መኖር፣ እነርሱ ከሰው ዘርም ከአጋንንትም ዓለም ያልሆኑ የስውር ዓለም ፍጡራን እንደሆኑ በቁርጠኝነት ማጽደቅ ነው፡፡ እነርሱ የተከበሩና አላህን ፈሪዎች ናቸው፡፡ አላህን ትክክለኛ የሆነ መገዛትን ይገዙታል፡፡ እርሱ ያዘዛቸውን በመፈፀም ያስተናብራሉ፡፡ በአላህ ላይ ፈፅሞ አያምጹም፡፡

አላህ (ሱ.ወ) እንዲህ ብሏል፡- «(መላእክት) የተከበሩ ባሮች ናቸው፡፡ በንግግር አይቀድሙትም (ያላለውን አይሉም) እነሱም በትዕዛዙ ይሰራሉ፡፡» (አል አንቢያ 26-27)

በእነሱ ማመን ከኢማን ስድስት መሠረቶች አንዱ መረት ነው፡፡ አላህ (ሱ.ወ) እንዲህ ብሏል፡- «መልክተኛው ከጌታው ወደርሱ በተወረደው አመነ፡ ምዕመናኖችም (እንደዚሁ) ሁሉም በአላህ በመላእክቱም በመጻሕፍትቱም በመልክተኞቹም…. አመኑ፡፡» (አል በቀራ 285) ኢማንን አስመልክተው ነቢዩ (ሰ.ዐ.ወ) እንዲህ ብለዋል፡ «በአላህ፣ በመላእክቱ፣ በመጽሐፍት፣ በመልዕክተኞች፣ በመጨረሻው ቀንና በክፉም በደጉም በአላህ ውሳኔ ልታምን ነው፡፡» (ሙስሊም 8)

በመላእክት ማመን ምንን ያካትታል?

  1. በመኖራቸው ማመን፡ እነርሱ የአላህ ፍጥረታት እንደሆኑ እናምናለን፡፡ በተጨባጭ ያሉ ናቸው፡፡ አላህ የፈጠራቸው ከብርሃን ነው፡፡ እርሱን በመገዛትና በመታዘዝ ላይ አግርቷቸዋል፡፡
  2. ከነርሱ መካከል እንደ ጂብሪል (ዐ.ሰ) በስሙ ያወቅነውን እስከነስሙ እናምናለን፡፡ በስማቸው ያላወቅነውናቸውንም በጥቅሉ እናምንባቸዋለን፡፡
  3. ከባህሪያቸው በምናውቀው ማመን፡፡ ከባህሪያቸው መካከል፡

እነርሱ የስውር ዓለም ፍጥረታት መሆናቸው፡፡ ለአላህ የሚገዙ ፍጡራን ናቸው፡፡ ከቶም የጌትነትም ሆነ የአምላክነት ባህሪ የላቸውም፡፡ እንደውም እነሱ አላህን ለመታዘዝ ሙሉ በሙሉ የተገሩ የአላህ ባሮች ናቸው፡፡ አላህ (ሱ.ወ) እንዲህ ብሏል፡- «አላህ ያዘዛቸውን በመጣስ አያምጡም፡፡ የሚታዘዙትንም ሁሉ ይሰራሉ፡፡» (አል ተህሪም 6)

የተፈጠሩት ከብርሃን ነው፡፡ ነቢዩ (ሰ.ዐ.ወ) እንዲህ ብለዋል፡ «መላእክት ከብርሃን ተፈጠሩ፡፡» ሙስሊም 2996

ክንፎች አሏቸው፡፡ አላህ (ሱ.ወ) ለመላእክት ክንፍን እንዳደረገ ተናግሯል፡፡ የክንፎቻቸው ብዛት ይበላለጣል፡፡ አላህ (ሱ.ወ) እንዲህ ብሏል፡- «ምስጋና ሰማያትንና ምድርን ፈጣሪ፣ መላእክትን ባለ ሁለት ሁለት፣ ባለ ሦስት ሦስትም፣ ባለ አራት አራትም ክንፎች የኾኑ መልክተኞች አድራጊ ለኾነው አላህ ይገባው፤ በፍጥረቱ ውስጥ የሚሻውን ይጨምራል፤ አላህ በነገሩ ሁሉ ላይ ቻይ ነውና፡፡» (ፋጢር 1)

  1. በአላህ ትዕዛዝ መሰረት እነርሱ ከሚያከናውኗቸው ስራዎቻቸው ባወቅነው ማመን፡፡ ከነርሱ መካከል፡-

መለኮታዊ ራዕይን ወደ መልክተኞች በማምጣት የተወከለ አለ፡፡ እሱም ጂብሪል (ዐ.ሰ) ነው፡፡

ነፍስን በማውጣት የተወከለም አለ፡፡ እርሱም የሞት መልአክና ተባባሪዎቹ ናቸው፡፡

መልካምም ሆነ እኩይ፣ የባሮችን ስራ መዝግቦ በማቆየት ወይም በመጠበቅ የተወከሉ አሉ፡፡ እነሱም የተከበሩ ፀሐፍት መላእክት ናቸው፡፡

በመላእክት የማመን ፍሬ ወይም ጥቅም፡፡

በመላእክት ማመን በሙእሚን ሕይወት ውስጥ ትልቅ ጥቅም አለው፡፡ ከነኚህ ጥቅሞች መካከል የሚከተሉትን እንጠቅሳለን፡፡

  1. የአላህን ልቅና፣ ኃይል፣ ሙሉዕነትና ችሎታ ያሳውቃል፡፡ የፍጥረታት ትልቅነት የፈጣሪያቸውን ትልቅነት ያሳያል፡፡ በመሆኑም አንድ ሙዕሚን በመላእክት በማመኑ ለአላህ የሚሰጠው ደረጃና ለርሱ ያለው ከበሬታ ይጨምራል፡፡ አላህ (ሱ.ወ) ብዙ ክንፎች ያሏቸው መላዕክትን ከብርሃን የፈጠረ ነው፡፡

  2. አላህን በመታዘዝ ላይ ጽናትን ያጎናጽፋል፡፡ መላዕክት ስራዎቹን በሙሉ እንደሚፅፉ የሚያምን ሰው፣ ይህ እምነቱ የአላህ ፍራቻ እንዲያድርበት ያደርጋል፡፡ በይፋም ሆነ በድብቅ በአላህ ላይ አያምጽም፡፡

  3. አንድ አማኝ በዚህ ሰፊ ዓለም ውስጥ አላህን የሚታዘዙ መላእክት አብረውት በተሟላና ባማረ መልኩ እንዳሉ በእርግጠኝነት በሚረዳ ጊዜ አላህን የመታዘዝ ትዕግስትን ይላበሳል፡፡ መላመድንና መረጋጋትን ያገኛል፡፡

  4. ከመላእክት መካከል የሚጠብቋቸውና የሚከላከሉላቸው በማድረግ አላህ ለአደም ልጆች በቸረው ትኩረቱና ክትትሉ ማመሰገን፡፡